Monday, 18 August 2014



  የውህደቱ ዓላማዎች
                                                             
                                                             አስራት አብርሃም

ተዋሃደ፣ አንድ ሆነ እንዲል መፅሐፉ፤ የአንድነትና የመኢአድ አባላት ዘመኑን በውህደት የሚጀምሩበትና አንድ የሚሆኑበት ቀን ላይ ደርሷል። በዚህም ምክንያትም አዲስ ፓርቲ፣ አዲስ ፕሮግራም እና አዲስ መሪ ይኖረን ዘንድ መልካም ፍቃዳቸው ሆኗል። ይህ ውህደት የጋራ ቤታችን ለሆነችው ለውዲቷ ሀገራችን ያለንን በጎ ምኞትና ሀሳብ የምንገልፅበት፤ እንደህዝብ ያሉንን ማህበራዊና ፖለቲካዊ ግንኙነቶች መልሰን የምናስተሳስርበት መልካም አጋጣሚ ነው ብዬ አስባለሁ። ውህደት ሲባል በተለያዩ ፓርቲዎች ውስጥ የነበሩትን አባላት ወደ አንድ ፓርቲ ማምጣት ማለት አይደለም፤ ሰዎች አይደለም እየተዋሃዱ ያሉት፤ እየተዋሃደ ያለው ሀገራዊ ዓላማ ራዕይ ነው። ለዚህ ሀገራዊ ዓላማና ራዕይ ሲባል ነው ሁለት የነበሩ ፓርቲዎች አንድ የሚሆኑት። በዚህ ምክንያት ደግሞ የፓርቲ አባላት ብቻ ሳይሆኑ ሀገር ነው የሚወሃደው፤ ኢትዮጵያውያን ናቸው በዜግነት ላይ በተመሰረተ የእኩልነትና የነፃነት መርህ የሚዋሃዱት።
ለመግቢያ ያህል እህን ካልኩኝ ለመሆኑ የውህደቱ መሰረታዊ አላማዎች ምንድናቸው? በሚለው ጉዳይ ላይ የተወሰነ ነገር ለማለት እፈልጋለሁ። ውህደቱ በዋናነት የተፈለገው ሁለቱም ፓርቲዎች በተናጥል ሊያሳኩት ያልቻሉትን ፖለቲካዊ ዓላማ አንድ ላይ ሆኖ ለማሳካትና ከግብ ለማድረስ በማሳብ ነው። ይህ ደግሞ በተቃዋሚዎች መካከል ያለውን ያለመታማመን መንፈስ ይህ ውህደት ምሳሌ በመሆን አብሮ አንድ ላይ ሆኖ እንዴት የተሻለ ነገር መስራት እንደሚቻል ለማሳየት ተነሳሽነቱ የመውሰድ ነገር ነው።በዚህም ምክንያት ይህ ውህደት የመጀመርያ እንዳልሆነ ሁሉ የመመጨረሻም አይሁንም ከአሀሁን በፊትም አንድነትና ብርሃን ያደረጉት ውህደት ብዙ ባይነገርለትም እጅግ በጣም የተሳካ እንደነበር መረዳት የሚቻል ነው። በቀጣይነትም በመድረክ ውስጥ ያሉ ወንድሞቻችና ሰማያዊዎች የዚህ ትልቅ ሀገራዊ የሆነ ፖለቲካዊ አቅም የመፍጠር ፕሮጀክት አካል ይሆናሉ ብዬ ነው የማስበው።
ዘላቂ የሆነ ፖለቲካዊ ለውጥ ማምጣት የምንችለው እውነተኛ የዴሞክራሲና የለውጥ ኃይሎች የሆኑትን ወደ አንድ የተጠናከረና የተደራጀ ኃይልነት መሸጋገር ሲችሉ ነው፤ ውድድሩም የሁለትዮሽ ብቻ ነው መሆን አለበት፤ በኢህአዴግና በአንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ፣ ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ እንደሚሉት በአውራ ገዥ ፓርቲና በዴሞክራሲያዊ አውራ ፓርቲ መካከል ነው መሆን ያለበት። ከዚህ ውጪ ያሉት ሌሎች ፓርቲዎች በክልልና በከተሞች ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ሊኖሩ ይችላሉ፤ ለምሳሌ የክልል ፓርቲዎች እንዳሉ ሁሉ አዲስ አበባና ድሬዳዋ የራሳቸው የሆኑ የከተማ ፖለቲካዊ ፓርቲዎች ሊኖራው ይችላል፤ ሀገራዊ የሆኑ ፓርቲዎች ግን ወደ አንድ ጠንካራና ዘላቂ ኃይል መሰባሰብ መቻል አለባቸው። በተመሳሳይ ሁኔታ ዴሞክራሲያዊው አውራ ፓርቲ ራሱን የቻለ ነፃነትና ያልተማከለ ስልጣን ያለው የክልልና የከተማ መዋቅር ይኖረው ዘንድ የተገባ ነው። በዚህ መንገድ ነው ከክልሎችም ሆነ ከከተማ ፓርቲዎች የተሻለ ሰፊ መዋቅርና ተደማጭነት እንዲኖረው የሚሆነው። ቀስ በቀስ ወደ ተረጋጋና ዘላቂነት ወዳለው ፖለቲካዊና ሀገራዊ ሁኔታ ለመምጣት ወደ ሁለት ፓርቲ ስርዓት መምጣት መቻል አለብን። ለዚህ ደግሞ ልዩ ልዩ ፍላጎቶቻችንን በማጣጣምና በማጠጋጋትና በእኩልነት መርህ ላይ የተመሰረተ ሰጥቶ የመቀበል ባሀል ማዳበር ይጠበቅብናል።
ሌላው ነገር በሀገራዊ አንድነት ስም የግልና የቡድን ፍላጎቶችን በሌላው ላይ ለመጫን ያለ መመኮር ነው። እንደዚሁም፣ ማንኛውም ሀገራዊ ጉዳይ ላይ በአንደኝነትና በሁለተኝነት የሚመለከተው ዜጋ ፈፅሞ መኖር የለበትም። እንደ ህዝብ የሚኖሩን ግንኝነቶች በእኩልነትና በነፃነት መርህ ላይ የተመሰረተ፣ መከባበርና መግባባት ያለበት መሆን አለበት። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ምን ዓይነት ታሪክ፣ ምን ዓይነት ስርዓትና ማንነት፣ ምን ዓይነት አስተዳደርና አከላለል ይኑራት በሚለው ጉዳይ ላይ የሁሉንም ፍላጎቶች ባጣጣመና በእውነታ ላይ የተመሰረተ፣ በእውቀት የተደገፈ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል።
ከሁሉም ነገር በላይ ደግሞ ማንም በማንም ላይ የሚጭነው ነገር መኖር የለበትም፤ ተወደደም ተጠላም ይሄ የጋራችን ቤት ነው። ከዚህ የተለየ ፍላጎት ያለው ሰው ወይም ቡድን ካለ በራሱ ክልል ወይም አከባቢ እዚያ በሚኖረው ህዝብ ዘንድ ተቀባይነት ካገኘ ማራመድ ይችላል። የአከባቢያዊነትና የሀገራዊ ፖለቲካ መደበላለቅ የለባቸውም፤ ብዙ ውዝንብር እንዲፈጠርና ውሀ ቅዳ ውሀ መልስ የሆነ ፖለቲካዊ ትግል እንዲኖር የሆነው በዚሁ የአከባቢያዊነትና የሀገራዊነት ፖለቲካ መደባላቅ ነው። እዚህ ሀገር በስም ደረጃ ሀገራዊያን የሆኑ በተግባርና በአመለካከት ግን አከባቢያዊ የሆኑ ፓርቲዎች ነበሩ፤ አሁንም አሉ። በመሆኑም የእኛ ትግልና አካሄድ ከዚህ በዓይነቱና በባህሪው የተለየ ነው መሆን ያለበት። በዚህ መንገድ የተጓዝን እንንደሆነ ብቻ ነው አዲሱን ውህድ ፓርቲ በልዩ ልዩ ባህልና ቋንቋ ያሸበረቀ ነገር ግን በፖለቲካዊ እምነት የሀሳብ አንድነት (Unity of Ideas) ባላቸው ዜጎች የተደራጀ፤ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የትግል መድረክ ማድረግ የምንችለው።
የውህደቱ ሁለተኛ ዓላማ የኢትዮጵያ ህዝብ በተቃዋዎች ላይ ያጣውን እምነት እንዲመለስና ለለውጥ እንዲነሳሳ ማድርግ ነው። ህዝቡ በተደጋጋሚ በፖለቲካ ፓርቲዎችና መሪዎች የተከዳ፤ በፓርቲዎች ውስጥ የሚያየው ሽኩቻና መከፋፋል እጅግ በጣም ተስፋ እንዲቆርጥ ያደረጉት በመሆኑ ይህን ቁስል እንዲሽር ለማድረግና ህዝቡን ለመካስ ከዚህ የተሻለ አጋጣሚ ሊገኝ አይችልም። በእርግጥ በሀገራችን ያሉት ፖለቲካዊ ችግሮች የተቃዋሚ ፓርቲዎቹ ብቻ ነው ማለት ባይቻልም ፓርቲዎቹ የአንበሳውን ድርሻ ስለሚወስዱ ነው። እንደ ህዝብ በፖለቲካዊ አመለካካት በኃይናማኖትና በቋንቋ  የተለያየ እንደመሆኑ መጠን ወደ እንድ ሊያሰባስበው የሚችል ሀገራዊ ሀሳብ አለመገኘቱ ነው አንዱ ችግር። ስለዚህ ይሄ ውህደት አንዱ ሊያሳካው ይችላል ተብሎ የሚታሰበው ይሄ የህዝቡን እምነት መመለስ ነው።
እነዚህና ሌች ዓላማዎች ይሳኩ ዘንድ ምን መደረግ አለበት በሚለው ርዕሰ ጉዳይ ላይ ደግሞ  የተወሰነ ነገር ልበል፤ ከሁሉም በላይ ጠንከራ የሆነ ሁሉንም ፍላጎቶች ሊያሰባስብ የሚችል መሪ ውህዱ ፓርቲ ሊኖረው ይገባል። የሁለቱም ፓርቲዎች ውህደት የራሱ የሆነ መለያ ያለው አዲስ ፓርቲ የሚወልድ እንደመሆኑ ለዚህ አዲስ ፓርቲ በብቃትና በሁሉም ነገር የሚመጥን አዲስ መሪ ያስፈልገዋል። አለበዚያ ውህደቱ አዲስ ወይን በአሮጌ አቅማዳ እንደመቋጠር ነው የሚሆነው።
ሁለተኛው የሀሳብ ነፃነትና ዴሞክራሲያዊ ባሀል እንዲገለብት ያላሰለሰ ጥረት ማድርግ መቻል ነው።
እንግዲህ የምንከተለው ርዕዮተ ዓለም ሊበራሊዝም ነው፤ ሊበራሊዝም ደደግሞ ነፃነትነና እኩልነት በሚሉ በሁለት ወሳኝ በሆኑ የዴሞክራሲ ምሶሶዎች ላይ የቆመ ነው። ነፃነት ሲባል አንድ ሰው ህሊናው የፈቀደለን በፈለገው ማዕቀፍ ውስጥ ሆኖ አቋሙንና ሀሳቡን በነፃነት ያለ ምንም መግለፅ ሲችል፤ በፈለገው ጉዳይ ላይ አቋም መያዝና የመሰለውን ሀሳብ ማራመድ ሲችል ነው። በምንም ዓይነት ሁኔታ ፍረጃ፣ ዘረኝነትና አሉባልታ የሊበራሊዝም መገለጫዎች ሊሆኑ አይችሉም። ሊበራሊዝም ራሳቸውን የቻሉ የሚተነተኑ እሴቶች ያሉት እንጂ እንደ ደብተራ ድጋም የማይታወቅ፣ የማይዘረዘርና የማይግባ ሚስጥር አይደለም። በተለይ ከፍረጃ ፖለቲካ ሙሉ ለሙሉ ለመላቀቅ የውህዱና የአዲሱ ፓርቲ አመራርና አባላት ቁርጠኛ የሆነ አቋም መውሰድ የሚጠበቅባቸው ነው።
ሌላው ደግሞ በአባላት መሀል የስልጣንና የመዋቅር ግንኙነት እንጂ የጌታና የሎሌ ግንኙነት መኖር የለበትም። እዚህ የሚመጣ ሁሉ በፓርቲው አላማና ፕሮግራም እንዲሁም ህገ ደንብ ምክንያት የመጣ፣ ለትግሉ ዓላማ ወዶና ፈቅዶ የተሰባሰበ እንጂ የእገሌ ቡድን ወይም የእገሌ አጋፋሪ ሆኖ የመጣ ይኖራል ብዬ አላስብም፤ ካለ ሎሌ ሆኖ የተሻለ ወደ ሚያገኝበት ቦታ ነው መሄድ ያለበት፤ ለምን በከንቱ ጊዜው ያጠፋል፤ ለምንስ በሁለት ይጎዳል ወይ ካላማው ወይ ከስጋ ካልሆነ! በዚህ ሀገር ትክክለኛ የሆነ ፖለቲካዊ ለውጥ እንዲመጣ ከተፈለገ ከኋላቀርና ከባህላዊ አመራር ለአንዴና ለመጨራሻ ጊዜ መቆራረጥ መቻል አለብን፤  አለበዚያ ልናመጣው እያሰብነው ያለው ፓርቲያዊ አሰራር ስኬታማ ላይሆን ይችላል።
አሉዋልታ፣ ሴረኝነት፣ የጀርባ  ስም አጥፊነት ፖለቲካ አይደለም፤ ርዕዮተ ዓለማችን ሊበራሊዘም ነው፤ ግልጽ መሆን፣ በሀሳብ ተከባብሮ መነጋገር፣ በሀሳብ ተለያይቶም መከባበር ማለት ነው። በእርግጥ በሀሳብ ለመከራከር መጀመርያ ሀሳብ ሊኖርህ ያስፈልጋል፤ “ኧረ ጎራው” በራሱ ፖለቲካ ሊሆን አይችልም! ፖለቲካዊ ውይይት ለማድረግ አሳማኝ የሆነ ሀሳብ መያዝ ያስፈልጋል፤ ነፃ ህሊና ያለው ሰው ሁሉ ሊቀበለውና ሊያምንበት የሚችል ማለት ነው።
እንደዚሁም ሰርጎ ገብነት፣ አስመሳይነትና አላማ የለሽነት መዋጋት፤ እስከመጨረሻ ድረስ ሄዶ ማስወገድ አስፈላጊ ነው። የሰርጎ ገብ ሰው መለያ ምንድነው ካለን ስራ ላይ አይገኝም ወሬ፣ ጥርጣሬ በፓርቲ ውስጥ እንዲነግስ ግን ጠንክሮ ይሰራል። ዋና አለማው በአባላት መሀል ጥርጣሬና ያለመተማመን መፍጠር ነው። ለዚህ መድሀኒቱ ደግሞ ማንኛውም ፓርቲ የሚመለከት ወሬ ወይም ሀሜት የሚያመጣል ሰው ከየት አገኘኸው? ማን ነገረህ? ብለን ማጣራትና ፊት ለፊት መግጠም ያስፈልጋል። አለበዚያ እንደ ብል ነው ፓርቲው ውስጥ ለውስጥ በሚብሰከሰክ ወሬና አሉዋለታ የሚፈርሰው። እንዲህ የሚያደርግ ሰው ገዥው ፓርቲ ባይከው እንኳ ሰርጎ ገብ ከመሆን አያመልጥም። ማንም ይላከው ማን በአፍራሽ እንቅስቀሴ ውስጥ እስከተገኘ ድረስ እርሱ ሰርጎ ገብ ነው ሊባል የሚችለው።
በመጨረሻ የምለው ነገር ቢኖር አዲስ ፖለቲካዊ ባህል፣ በመከባበር ላይ የመሰረተ ፖለቲካዊ አሰራር ነው መትከል ያለብን። ከአሁን በፊት ከነበሩ ውህደቶችና ቅንጅቶች ውድቀትና ስኬት ተምረን የተሻለ ተቋማዊ አሰራር መፍጠር  አለብን። በተለይ ደግሞ ከሁሉም ነገር በላይ ከግለሰቦች ፍላጎትና ተፅዕኖ ገለልተኛ የሆነ፣ አንድን ግለሰብ ወይም ቡድን ለማጥቃት የማያስችል ፓርቲያዊ ስርዓት መፍጠር ያስፈልገናል፤ በዚህ መንገድ የተጓዝን ከሆነ  ብቻ ነው ውህደቱ ዘላቂና ውጤታማ ሊሆን የሚችለው።      


No comments:

Post a Comment